
ዶ/ር ፍራንክ ዋልተር ስተይንመር፣ የጀርመን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር
የጀርመን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዶ/ር ፍራንክ ዋልተር ስተይንመር የአንድ ቀን የኢትዮጵያ ጉብኝት፣ በመንግሥት ባለሥልጣናትና በመንግሥት ሚዲያዎች ከፍተኛ ትኩረት የተሰጠው ነበር፡፡
(ሪፖርተር) ዶ/ር ስተይንመር ከጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ፣ ከፕሬዚዳንት ሙላቱ ተሾመና ከውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ዶ/ር ቴድሮስ አድሃኖም ጋር ተገናኝተው በሁለትዮሽ ግንኙነትና በአካባቢያዊ የደኅንነት ወቅታዊ ጉዳዮች ላይ መምከራቸው፣ ጀርመን ለኢትዮጵያ ያላት ግምት ከፍተኛ መሆኑን አመላካች ነው፡፡
በአፍሪካ በሦስት አገሮች ወሳኝ የተባለለትን ጉብኝታቸውን በኢትዮጵያ የጀመሩት ዶ/ር ስተይንመር፣ አገራቸው ከኢትዮጵያ ጋር የምታደርገው ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ትብብር ከሁለትዮሽ ግንኙነት በላይ መሆኑ አመላካች እንደሆነ ለጋዜጠኞች ተናግረዋል፡፡
በጀርመን ከመራሄ መንግሥት አንገላ መርከል ቀጥለው ወሳኝ እንደሆኑ ተደርገው የሚታዩት ዶ/ር ስተይንመር፣ አንድ ትልቅ የባለሀብቶች ቡድን መርተው የመጡ ሲሆን፣ መንግሥታቸው በኢትዮጵያ ያየው ከፍተኛ የኢኮኖሚ ዕድገት ኢንቨስትመንት እንዲያፈስ አነሳስቶታል፡፡
የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ከአቻቸው ከዶ/ር ቴድሮስ ጋር ከመከሩ በኋላ ማክሰኞ ረፋዱ ላይ ለጋዜጠኞች በጋራ በሰጡት መግለጫ፣ ኢትዮጵያ በአፍሪካ አኅጉር በራሷ የምትቆምና በራሷ የምትተማመን አገር ሆና ማየት እንደሚፈልጉ ገልጸው፣ ‹‹የመድበለ ፓርቲ ሥርዓት የሰፈነባት፣ የሲቪክ ማኅበረሰቦች በነፃ የሚንቀሳቀሱባትና ሰዎች በነፃነት ሐሳባቸውን የሚገልጹባት አገር ሆና ማየት እፈልጋለሁ፤›› ሲሉ ምኞታቸውን ተናግረዋል፡፡ ሙሉውን ሪፖርተር ላይ ለማንበብ ይሄን ይጫኑ