Tuesday, December 5, 2023
HomeEthiopian Newsየ ካራሎ የሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ተማሪ በፖሊስ ላይ ተኮሰ

የ ካራሎ የሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ተማሪ በፖሊስ ላይ ተኮሰ

(ፍኖተ ነጻነት) በአዲስ አበባ ካራሎ አካባቢ በሚገኘው ካራሎ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት የዘጠነኛ ክፍል ተማሪ መሆኑ የተነገረለት ተሾመ አረጋ ታጥቆት ወደ ትምህርት ቤት እንደመጣ በተነገረለት ሽጉጥ አንድን ፖሊስ ለመምታት ተኩሶ ፖሊሱ መሬት ላይ በመተኛቱ ህይወቱ መትረፉን የፍኖተ ነጻነት የመረጃ ምንጮች አስታወቁ፡፡

በቅርቡ በተከበረው የጥምቀት በዓል በካራሉ ተፈጥሮ በነበረ የቡድን ጸብ በመደብደቡና በጩቤ በመወጋቱ ቂም ቋጥሮ የከረመው ተሾመ ለጊዜው በምን መንገድና ከማን እንዳገኘው ያልታወቀን ሽጉጥ በመያዝ ጉዳት ያደረሱበትን ወጣቶች ለመበቀል በማሰብ ወደ ትምህርት ቤቱ ይመጣል ፣ትምህርት ቤቱ ፈተና ለተማሪዎቹ በሚያዘጋጅበት ወቅት ሁልግዜም የተማሪዎቹን ደህንነት ለመጠበቅ የፖሊስ እርዳታን እንደሚጠይቅ የሚናገሩት ምክትል ርዕሰ መስተዳድሩ አቶ ጌታቸው ታምሩ በዛሬው ዕለትም በአካባቢው ፖሊሶች በመገኘታቸው ተሾመ በያዘው ሽጉጥ አደጋ ከመፍጠሩ በፊት ፖሊሶች ማክሸፋቸውን ለፍኖተ ነጻነት አስታውቀዋል፡፡

ተሾመ ወደ ትምህርት ቤቱ ከመግባቱ በፊት ግርግር በመፈጠሩ ፖሊሶች የግርግሩ ፈጣሪ እንደሆነ የተረዱትን ተማሪ ለመያዝ ሲጠጉ ተሾመ ሽጉጡን በማውጣት እንዳይጠጉት በማስጠንቀቅ ሩጫ ይጀምራል፣ ፖሊሶቹ ተማሪውን ለመያዝ በሩጫ ሲከተሉትም ተማሪው አንደኛውን ፖሊስ ለመምታት ይተኩሳል፣ በስፍራው የነበሩ የአይን እማኞች እንደተናገሩት ከሆነ ሽጉጥ የተተኮሰበት ፖሊስ መሬት ላይ በመውደቁ ከአደጋው ለማምለጥ ችሏል፡፡

የተማሪው ወላጅ አባት በፖሊስ ቁጥጥር ስር መዋላቸውን የሚገልጹት ምንጮቻችን ተሾመም ከጥቂት ሰዓታት መሰወር በኋላ በፖሊስ መያዙን ገልጸዋል፡፡ክስተቱ በተማሪዎች ስነ ልቦና ላይ ጭንቀት የሚፈጥር በመሆኑ ፈተናቸውን በሌላ ጊዜ እንዲወስዱ ስለማድረጋቸው የተጠየቁት ምክትል ርዕሰ መምህሩ ‹‹በተማሪዎቻችን ላይ ምንም አይነት ጭንቀት ባለመፈጠሩ ፈተናቸውን እንዲወስዱ አድርገናል፡፡››ብለዋል፡፡

ስለዘገባው የበለጠ ለማወቅ ይሄን ይጫኑ

advertisment

LEAVE A REPLY

Please enter your comment!
Please enter your name here